ሱዳን በኡጋንዳ ላይ ጠንካራ ትችት ሰነዘረች፡፡

ኢትዮ ሞኒተር፡ 16/06/2018፡- የሱዳን መንግስት፤ ዩጋንዳ የተቀናቃኙን የፈጥኖ ደራሽ ኃይሎች መሪ መሐመድ ሀምዳን ዳግሎን (ሄሜቲ) ማነጋገሯን በመቃወም በካምፓላ ላይ ትችት ሰነዘረ።
የዩጋንዳው ፕሬዝዳንት ለመሪው ያደረጉትን አቀባበልም በሰብዓዊነት ክብር ላይ የተፈጸመ ድርጊት ሲልም በካምፓላ ላይ ጠንካራ ትችት ሰንዝሯል።
ይህ የካምፓላ ጉብኝት የተከናወነው በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የባለሙያዎች ቡድን የፈጥኖ ደራሽ ኃይሎች በዳርፉር የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸማቸውን የሚያመላክት ሪፖርት ይፋ ባደረገ ማግስት ነው።
የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለጸው፣ ሄሜቲ የሚመሩት ኃይል የሚፈጽማቸው የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ የታወቁ ከመሆናቸው ባለፈ፣ ዩጋንዳ አባል በሆነችባቸው እንደ አፍሪካ ሕብረት እና ኢጋድ ባሉ ቀጠናዊ ድርጅቶች ጭምር የተወገዙ ናቸው።
በሌላ በኩል ሄሜቲ ለደጋፊዎቻቸው ባደረጉት ንግግር ወደ ዩጋንዳ ያቀኑት ለፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ የቀረበውን የማስታረቅ ጥያቄ ተከትሎ መሆኑን ገልጸዋል። መሪው በንግግራቸው ወቅት ለሱዳን ሰላም አፍሪካዊ መፍትሄ እንደሚያስፈልግ አጽንኦት የሰጡ ሲሆን፣ የሽምግልና ጥረቱም በአፍሪካ ሕብረት እና በኢጋድ በኩል መመራት እንዳለበት ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የካምፓላው ቆይታ ሙሴቬኒ የሉዓላዊ ምክር ቤቱ ምክትል የሆኑትን ማሊክ አጋርን ካስተናገዱ ከአንድ ሳምንት በኋላ የተከናወነ በመሆኑ፣ ዩጋንዳ በሁለቱም ወገኖች መካከል ሚዛን ለመጠበቅ እየሞከረች እንደሆነ ይገመታል።
በግንባር ስላለው ሁኔታ ማብራሪያ የሰጡት ዳግሎ፣ አሁን ያለውን ግጭት “የህልውና ጦርነት” ሲሉ የገለጹት ሲሆን፣ የግብፅ እና የቱርክ የሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) ጣልቃ ገብነት ባይኖር ኖሮ ካርቱምን እና ፖርት ሱዳንን መቆጣጠር ይችሉ እንደነበር ተናግረዋል።
አያይዘውም በብሉ ናይል በኩል ያሏቸው ኃይሎች በጥሩ አቋም ላይ እንደሚገኙ የገለጹ ሲሆን፣ ይህ ከኢትዮጵያ ጋር በሚዋሰነው ድንበር አካባቢ የተከፈተው አዲስ ወታደራዊ እንቅስቃሴ የቀጠናውን ስጋት ይበልጥ አባብሶታል።



