አፍሪካ
ጄኔራል አልብሩሀን ለተኩስ አቁም 4 ቅድመ ሁኔታዎችን ማቅረባቸው ተሰማ፡፡
በሱዳን ውስጥ ያለውን የእርስ በእርስ ጦርነት ለማስቆም በ4 አገራት መካከል አዲስ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል፡፡

ኢትዮ ሞኒተር፡ 05/03/2018፡- በአሜሪካ፣ በሳኡዲ አረቢያ፣ በዩናይትድ አረብ ኤመሬትስና በግብፅ አማካኝነት እየተካሄደ ያለው ይህ ጥረት ምክረ ሀሳብ ያቀረበ ሲሆን በዚህም በአስቸኳይ የ3 ወራት የሰብአዊነት ተኩስ አቁም እንዲደረግና፣ በ9 ወራት ውስጥ ደግሞ ሁለቱም ተፋላሚዎች የማይሳተፉበት የፖለቲካ ሂደት እንዲጀመር ጠይቆ ነበር፡፡
ይህንን ምክረ ሀሳብ የጄኔራል አብዱል ፈታህ አልብሩሀን መንግስት ውድቅ ሲያደርገው ተቀናቃኙ ፈጥኖ ደራሽ ሀይል ግን እንደሚቀበለው መግለፁ ይታወሳል፡፡
አልሱዳኒ የተሰኘው ጋዜጣ ዛሬ እንደዘገበው ደግሞ የሌተና ጄኔራል አልብሩሀን መንግስት በአራትዮሽ አደራዳሪዎቹ በቀረበው ምክረ ሀሳብ ላይ እንደሚስማማ አስታውቋል፡፡
ነገር ግን ምክረ ሀሳብ ለመቀበል 4 ቅድመ ሁኔታዎችን ለአደራዳሪዎቹ ማቅረቡን የጠቀሰው ዘገባው እነዚህም፤ ፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ በቅርቡ ከያዛቸው አካባቢዎች ለቆ እንዲወጣ፣ የፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ ታጣቂዎች በሚዘጋጅላቸው ካምፕ ውስጥ እንዲገቡ፣ ፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ ለቆ በሚወጣባቸው አካባቢዎች የፖሊስ ሀይል እንዲሰማራ እና የተኩስ አቁሙንና በፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ ላይ የተጣለውን የጦር መሳሪያ ገደብ የሚቆጣጠር አለም አቀፍ ታዛቢ ቡድን እንዲሰማራ የሚሉ መሆናቸውን አስረድቷል፡፡



