አፍሪካ
የአሜሪካ መንግስት ሶማሊያ ከ አልሸባብ እና አይኤስ ጋር በምታደርገው ውጊያ የሚሰጠውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አዲሱ የአፍሪኮም አዛዥ አረጋገጡ።

ኢትዮ ሞኒተር፡ 30/12/2017፡- በአፍሪካ የአሜሪካ ወታደራዊ ዕዝ (AFRICOM) አዲሱ አዛዥ ጄኔራል ዳግቪን አንደርሰን ረቡዕ እለት በሞቃዲሾ ከፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ ሞሀሙድ ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ፣ ሶማሊያ ከአልሸባብ እና አይኤስ የሽብር ቡድኖች ጋር በምታደርገው ውጊያ አሜሪካ የምታደርገውን ድጋፍ እንደምትቀጥል ቃል መግባታቸው ተገለጸ።
ጄኔራሉ ለአልሸባብ እና አይኤስ የሽብር ቡድኖች የተነደፈውን የአፍሪኮም የፀረ-ሽብር ስትራቴጂ ለፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ ማብራሪያ ያደረጉ ሲሆን፣ ዋሽንግተን የአየር ጥቃቶችን፣ የመረጃ ልውውጥን፣ ወታደራዊ ስልጠናን እና የሶማሊያ ብሔራዊ ጦርን ለማጠናከር ሰፋ ያለ ድጋፍ በማድረግ ትብብሯን እንደምታጠናክር መናገራቸውን ሂራን ዘግቧል።
ውይይቱ በተጨማሪም በአፍሪካ ቀንድ ቀጠና ያለውን የጸጥታ ሁኔታ፣ ድንበር አቋርጠው በሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ቡድኖች የሚመጣውን ስጋት እና ጠንካራ ቀጠናዊ ትብብር አስፈላጊነትንም ያካተተ እንደነበረ ዘገባው አመልክቷል።
ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ በበኩላቸው በአፍሪካ የአሜሪካ ወታደራዊ ዕዝ ለሶማሊያ ያለው አጋርነት ወሳኝ መሆኑን ገልፀው ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በተጨማሪም መንግስታቸው በሶማሊያ እና በቀጠናው ሰላምና መረጋጋትን ለማምጣት እንዲሁም ዓለም አቀፍ ትብብርን ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።