
ኢትዮ ሞኒተር፡ 21/11/2017፡ በሀገራዊ ምክክሩ ከተሳተፉ አመራሮች ውስጥ በአፋር ክልል የካቢኔ አባላት፣ የክልሉ ምክር ቤት አባላት እና የፀጥታ አካላት ጭምር ወደ ኤርትራ ገብተው ትጥቅ ትግል መጀመራቸውን ተሰምቷል።
ይህ የተገለጸው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ደርጅቶች ሕብረት ከሰሞኑ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ሂደት ዙሪያ የመጀመሪያ ዙር ክትትል ሪፖርቱን ባቀረበበት ወቅት ነው።
ሕብረቱ ያቀረበው የመጀመሪያ ዙር ሪፖርት እስከ መጋቢት መጨረሻ 2017 ዓ.ም ድረስ በተከናወኑ የሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ቁልፍ ግኝቶች ላይ ትኩረቱን አድርጓል።
በዚህ ሪፖርት በአማራ እና ትግራይ ክልሎች ከዚህ ቀደም በግጭት ምክንያት አጀንዳ ማሰባሰብ ያልተቻለበት ሁኔታ መፈጠሩን የተገለፀ ሲሆን፤ “አሁን ደግሞ በአፋር ክልል በምክክር ሂደት የነበሩ ሰዎች ጭምር ወደ ጫካ እየገቡ ነው” ተብለዋል፡፡
ከመንግሥት ኃላፊዎች በተጨማሪ ወደ ኤርትራ የተሻገሩ የሕብረተስብ ክፍሎች ጭምር መኖራቸውን የተገለጸ ሲሆን፤ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ይህንን ጉዳይ መመልከት እንዳለበት አፅዕኖት ተሰጥቶታል፡፡
የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሀገሪቱ በተለያዩ አካባባዎች ላሉ ታጣቂዎች ተደጋጋሚ ጥሪን ያቀረበ ቢሆንም፤ ጥሪውን ተቀብሎ ወደ ምክክሩ የመጣ እስካሁን አልተገኘም፡፡