
ኢትዮሞኒተር፡ 27/10/2017፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በትግራይ ክልል አሁን ላይ ምክክር ለማድረግ የሚያስችል ሁኔታ ባለመፈጠሩ ሥራዬ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አድርጎብኛል ሲል አስታውቋል።
ኮሚሽኑ በዛሬው ዕለት ለመገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ፤ በክልሉ ሀገራዊ ምክክር ለማስጀመር እየተሰሩ ባሉ ሥራዎች ዙሪያ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ሲያድረግ መቆየቱን ገልጿል።
የኮሚሽኑ ቃል አቀባይና የዋና ኮሚሽነሩ ልዩ አማካሪ አቶ ጥበቡ ታደሠ፤ በክልሉ ምክክር ለማድረግ ግልፅ ደብዳቤ ለትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በመላክ ምላሽ እየተጠበቀ እንደሚገኝ የገልጿል። ይህ ጥሪ በተጋጋሚ ጊዜ ሲደረግ መቆየቱም ጠቁሟል።
“ይሁን እንጂ በክልሉ እስካሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ አጀንዳ ማሰባሰብ የሚያስችል ሁኔታ ላይ አይደለንም” ሲሉ አቶ ጥበቡ ታደሠ በመግለጫቸው አንስተዋል።
ከምክክሩ ካቋረጡ ፖርቲዎቸ ጋር ውይይት በማድረግ ወደ ሂደቱ እንዲመለሱ ከሦስት ፖርቲዎች ማለትም እናት ፖርቲ፣ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፖርቲ (ኢህአፓ) ጋር ተወያየተዉ እንዲመለሱ እየተሰራ ስለመሆኑም አስታውቋል።
“እስካሁን ያልተሳተፉ ፖርቲዎች ኮከስ መስረተው የሚንቀሳቀሱ ናቸው” ያሉት የምክክር ኮሚሽኑ ቃል አቀባይ፤ “ወደ ምክክር እንዲመጡ ለማረድረግ ጥረት እየተደረገ ነው” ብለዋል።