
ኢትዮ ሞኒተር፡ 19/05/2018፡- ኡጋንዳ ለሁለት አስርት ዓመታት ያህል ተከታታይ የሰላም ማስከበር ስራዎችን ካከናወነች በኋላ ወታደሮቿን ከሶማሊያ የማስወጣት እቅድ እንዳላት አስታውቃለች።
ይህም እርምጃ ለቀጠናው ደህንነት እና ከአሸባሪው ቡድን አል_ሻባብ ጋር በሚደረገው ውጊያ ላይ ጉልህ አንድምታ ሊኖረው ይችላል ተብሏል።
የዩጋንዳ የጦር ኃይሎች ዋና አዛዥ ጄኔራል ሙሁዚ ካይኔሩጋባ እሁድ እለት በኤክስ ላይ ባወጡት አጭር መግለጫ፣ የአገሪቱ ወታደራዊ ተልዕኮ በሶማሊያ ውጤታማ በሆነ መንገድ ማብቃቱን እና አሁን ሙሉ በሙሉ ወታደሮቹ እንዲወጡ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
“ከ19 ዓመታት በሶማሊያ ቆይታ በኋላ ከዚያች ሀገር ሙሉ በሙሉ ለመውጣት በቅርቡ እንፈልጋለን” ሲሉ ሙሁዚ ተጨማሪ ዝርዝሮችን ወይም የጊዜ ሰሌዳ ሳይሰጡ ተናግረዋል።
የኡጋንዳ ወታደሮች በሶማሊያ የአፍሪካ ህብረት የድጋፍ እና የማረጋጋት ተልዕኮ ውስጥ ትልቁ ጦር ሲሆኑ፣ የአደን አዴ አለም አቀፍ አየር ማረፊያ፣ የሞቃዲሾ ወደብ እና በዋና ከተማዋ ውስጥ ያሉ ሌሎች ስትራቴጂካዊ ቦታዎችን ጨምሮ ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን በማስጠበቅ ረገድ ማዕከላዊ ሚና ተጫውተዋል።
በሶማሊያ ውስጥ የሚገኙትን የዩጋንዳ ወታደሮች ቁጥር ከ5,000 እስከ 6,000 እንደሚደርሱ ይገመታል። ኡጋንዳ ከ2007 ጀምሮ በአፍሪካ ህብረት ተልዕኮ ስር ወታደሮችን ያሰማራች የመጀመሪያዋ ሀገር ከሆነችበት ጊዜ ጀምሮ በሶማሊያ ውስጥ ለዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ጥረቶች መሰረት እንደሆነች ይገለፃል።
ባለፉት ዓመታት የኡጋንዳ ጦር የሰው ኃይል ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የአዛዥነት አመራርንም በመስጠት አልሸባብን ለመግታት እና የሶማሊያ የደህንነት ተቋማትን እንደገና ለመገንባት ድጋፍ ማድረጓ ተጠቅሷል።



