“አውሮፓ ከሩሲያ ጋር ግጭት ብትጀምር፣ ሩሲያ ወዲያውኑ ለመፋለም ዝግጁ ናት” ሲሉ ፕሬዝዳን ፑቲን ተናገሩ።

ኢትዮ ሞኒተር፡ 25/03/2018፡- የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በሞስኮ በተካሄደ የኢንቨስትመንት ፎረም ላይ ተገኝተው፣ አውሮፓ ከሩሲያ ጋር ግጭት ብትጀምር፣ ሩሲያ ወዲያውኑ ለመፋለም ዝግጁ መሆኗን እና የውጤቱ ከባድነት “ሰላም ለመደራደር የሚቀር ማንም እንዳይኖር” ሊያደርግ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።
ፕሬዝዳንቱ አውሮፓን የማጥቃት ዕቅድ እንደሌላቸው ቢገልጹም፣ “አውሮፓ በድንገት ከእኛ ጋር ጦርነት ለመጀመር ከፈለገች እና ከጀመረች፣ ያኔ ሁኔታው በፍጥነት ሊለወጥና የምንደራደርበት ማንም ሰው ላይቀር ይችላል” ብለዋል።
በዩክሬን እየተደረገ ያለው ጦርነት “ሙሉ-ደረጃ” እንዳልሆነ ገልጸው፣ የሩሲያ እርምጃ “የቀዶ ጥገና” ዓይነት ነው ቢሉም፣ ከአውሮፓ ጋር በቀጥታ በሚደረግ ግጭት ግን ይህ አካሄድ እንደማይሆን አሳስበዋል።
ፑቲን የአውሮፓ መሪዎችን የሰላም ጥረቶችን በማደናቀፍ የከሰሱ ሲሆን አውሮፓውያን “በፍጹም ተቀባይነት የሌላቸውን ጥያቄዎች” ወደ ድርድር ረቂቆች በማስገባት የአሜሪካን አስተዳደር ግጭቱን እንዳያቆም እየከለከሉ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
“የሰላም አጀንዳ የላቸውም፣ የጦርነት ወገን ናቸው” ሲሉም ከሰዋል።
የፑቲን ማስጠንቀቂያ የመጣው፣ የአሜሪካው ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ እና የዶናልድ ትራምፕ አማች ጃሬድ ኩሽነር የዩክሬን ግጭትን ለመቋጨት የዘመነውን የአሜሪካ የሰላም ዕቅድ ረቂቅ ይዘው ሞስኮ ውስጥ ከፑቲን ጋር የረጅም ሰዓታት ውይይት ካደረጉ በኋላ ነው።
የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ በውይይቱ ላይ “እስካሁን ድረስ መግባባት አልተደረሰም” ሲሉ ገልጸዋል፤ ነገር ግን ግጭቱን ለመፍታት “በኋላም ሆነ ቀደም ብሎ ስምምነት ላይ መድረስ ይቻላል” ብለዋል።
በውይይቱ የሩሲያ እና አሜሪካ ተደራዳሪዎች በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ልዩነት ማጥበብ አለመቻላቸው ተዘግቧል።



