አፍሪካ
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሱዳን ውስጥ የሚደረገው የሰብዓዊ ዕርዳታ ተደራሽነት ያለገደብ እንዲፈቀድ ጠየቀ።

ኢትዮ ሞኒተር፡ 23/03/2018፡- የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሱዳን የሚገኙ ሁሉም ወገኖች ለሰላማዊ ሰዎች እና ለእርዳታ ሰራተኞች “ደህንነቱ የተጠበቀና ያልተገደበ የሰብዓዊ ዕርዳታ ተደራሽነት” እንዲያረጋግጡ አስቸኳይ ጥሪውን አቅርቧል።
ተመድ ጥሪውን ያቀረበው የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል የሚፈፅማቸው ጥቃቶች ከፍተኛ የሰዎች መፈናቀልን በቀጠሉበት በአሁኑ ወቅት ነው።
የድርጅቱ ቃል አቀባይ ስቴፋን ዱጃሪክ ሰኞ ዕለት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፥ “ሰላማዊ ሰዎችን፣ የእርዳታ ሰራተኞችን ለመጠበቅ ሲባል ደህንነቱ የተጠበቀና ያልተገደበ የሰብዓዊ ዕርዳታ ተደራሽነትን በአስቸኳይ እንዲያረጋግጡ ሁሉንም ወገኖች በድጋሚ እንጠይቃለን” ብለዋል።
እንደ እርሳቸው ገለፃ፣ የተመድ የሰብዓዊ ዕርዳታ ቡድኖች በቅርቡ መጠለያ፣ አስፈላጊ ቁሳቁሶች፣ የጤና አገልግሎት እና የንፅህና አጠባበቅ ድጋፍ በአስቸኳይ የሚያስፈልጋቸውን ተፈናቃይ ቤተሰቦች አግኝተዋል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብ እና የስነልቦና ድጋፍ እየሰጠ ቢሆንም፣ “የገንዘብ እጥረት ክፍተቶችን ፈጥሯል” በማለት አስጠንቅቀዋል።
በመሆኑም ለጋሾች ተጨማሪ ድጋፎችን ለማቅረብ ቁርጠኛ እንዲሆኑ አጽንዖት ሰጥተዋል።



