
ኢትዮ ሞኒተር፡ 08/12/2017፡ ዓመታዊው የአሜሪካ የሰብዓዊ መብቶች አያያዝ ሪፖርት በ ኢትዮጵያ ከህግ ውጭ ግድያዎች፣ ማሰቃየት፣ የጅምላ እስራት መፈጸማቸውን አመላከቷል።
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ይፋ ባደረገው የ2024 የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ሪፖርት፤ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች በመካሄድ ላይ ባሉት ግጭቶች በመንግስት እና መንግስታዊ ባልሆኑ አካላት መጠነ ሰፊ የመብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን ገልጿል።
ሪፖርቱ በምዕራብ ትግራይ በአማራ ሚሊሻዎች እና አጋሮቻቸው ፤ “በርካታ የሲቪሎች ግድያ፣ በጅምላ ማፈናቀል፣ የዘር ማጽዳት፣ በሴቶች እና ልጃገረዶች ላይ የሚፈጸሙ አስገድዶ መድፈር እና ሌሎች ጥቃቶች፣ ዝርፊያ እና የንብረት ውድመት” መፈጸማቸውን ጠቅሷል።
በተጨማሪም በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች እንዲሁም በሌሎች አካባቢዎች “በሲቪሎች እና በመንግስት ባለስልጣናት ላይ መጠነ ሰፊ ከህግ ውጭ ግድያዎችን” መፈጸማቸውን ገልጿል። ለእነዚህ ድርጊቶች የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት እና የአማራ ፋኖ ታጣቂዎችን ተጠያቂ አድርጓል።
በሪፖርቱ መሠረት፣ በአፋር፣ አማራ፣ ኦሮሚያ፣ ጋምቤላ እና ሶማሌ ክልሎች የሚገኙ የሚሊሻ ቡድኖች “በሲቪሎች ላይ ጥቃት እና ግድያ በመፈጸም በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን አፈናቅለዋል”።
በተጨማሪም “በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች እንዲሁም ትግራይን ጨምሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች በግጭት አውድ ውስጥ በርካታ ሰዎች ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ መገደላቸውን” ሪፖርቱ ይገልጻል።
በአማራ ታጣቂ ሐይሎች ስር በሚገኘው የትግራይ ምዕራባዊ ዞን እስካሁን የዘር ማፅዳት ወንጀል እየተፈፀመ እንደሆነ ጠቁሟል።