
ኢትዮ ሞኒተር፡ 10/11/2017፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፌደራል ገቢ ግብር አዋጅን ለማሻሻል በቀረበ ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቶ አጸደቀ።
ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው ሁለተኛ አስቸኳይ ስብሰባ ነው የተሻሻውን አዋጅ ያጸደቀው።
በምክር ቤቱ የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ÷ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የገቢ ግብር አዋጅ ዲጂታል ኢኮኖሚውን ታሳቢ ያላደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት በአዋጁ ላይ የተደረገው ማሻሻያ ከዲጂታል ኢኮኖሚው ጋር የተጣጣመ ዘመናዊ የታክስ ሥርዓት ለመፍጠር ያስችላል ብለዋል።
የታክስ መሰረትን በማስፋት የመንግስትን የገቢ መሰብሰብ አቅም ለማሳደግ እንዲሁም የታክስ ማጭበርበርን ለመቀነስ ጉልህ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል።
የገንዘብ ሚኒስትር ዴዔታ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በበኩላቸው የማሻሻያ አዋጁ ተለዋዋጭ የሆነውን የኢኮኖሚ ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ የገቢ ግብር እንደ ሀገር ለታቀደው የኢኮኖሚ እድገት እውን መሆኑ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
መንግስት የዝቅተኛ ደመወዝ ተከፋዮችን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል የተለያዩ ርምጃዎችን እየወሰደ መሆኑንና ከገቢ ግብር አሰባሰብ ጋር ተያይዞ የሚፈጥረው ጫና አለመኖሩን አረጋግጠዋል።
የማሻሻያ አዋጁ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንትን ለመሳብና ለማበረታታት፣ የታክስ ማጭበርበርን ለመቀነስ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወትም አመልክተዋል።
በተጨማሪም ምክር ቤቱ የስታርታፕ አዋጅ ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብን መርምሮ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡