
ኢትዮ ሞኒተር፡ 02/10/17፡-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሩዋንዳ ኪጋሊ ያደረገውን 50ኛ አመት በረራ አክብሯል። እ.ኤ.አ. በ1975 የተጀመረው የአዲስ አበባ-ኪጋሊ መስመር በሁለቱ ሀገራት መካከል ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ባህላዊ ግንኙነቶችን ለመፍጠር ትልቅ አስተዋፅዖ እንዳለው የምስረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ የወጣው መግለጫ አመልክቷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው፥ ዝግጅቱ የግማሽ ምዕተ ዓመት ቁርጠኝነትን የሚያንፀባርቅ መሆኑን ጠቁመዋል። “እንዲህ ያለ ምዕራፍ ላይ በመድረሳችን በጣም ደስ ብሎናል፣ ለኪጋሊ ከ50 ዓመታት በላይ በማገልገል የመንገደኞችንም ሆነ የእቃ ማጓጓዣ ስራዎቻችንን አስፋፍተናል፣ ለደንበኞቻችን ጥቅም ድግግሞሹን ጨምረናል። ይህም የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካን ህዝብ ለማገልገል ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሌላ ማሳያ ነው” ብለዋል።
አየር መንገዱ ወደ ኪጋሊ 21 ሳምንታዊ የመንገደኞች በረራ እና ሶስት ልዩ የካርጎ አገልግሎቶችን እንደሚያደርግ ተገልጿል።